Asset Publisher

null ሙስና፤ ሀገራዊ ወጭን በሀገራዊ ገቢ ለመሸፈን የያዝነውን እቅድ ለማሳካት የምናደርገውን ጥረት የሚፈትን በመሆኑ የጸረ ሙስና ትግሉን አጠናክረን እንቀጥላለን ፡- የገቢዎች ሚኒስትር ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ

                                      (ጉምሩክ ኮሚሽን፣ ህዳር 24 ቀን 2016 ዓ.ም)
የገቢዎች ሚኒስቴርና የጉምሩክ ኮሚሽን አመራሮችና ሰራተኞች ߵߵሙስና የጋራ ጠላታችን ነው፣ በህብረት እንታገል ߴߴ በሚል መሪ ቃል በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ20ኛ ፣ በኢትዮጵያ ለ19ኛ ጊዜ እየተከበረ የሚገኘውን የጸረ ሙስና ቀን በጋራ አክብረዋል፡፡

በእለቱ ፕሮግራም የገቢዎች ሚኒስትር ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ፣ የፌደራል የስነ ምግባርና የጸረ ሙስና ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር እሸቴ አስፋው፣ ሚኒስትር ዴኤታዎች፣ ምክትል ኮሚሽነሮች እና የሁለቱም ተቋማት አመራሮችና ሰራተኞች ተገኝተዋል፡፡

ፕሮግራሙን በንግግር የከፈቱት ሚኒስትሯ ፣ ሙስና የሀገርን ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊና ፖለቲካዊ እንቅስቃሴን በማናጋት ሀገርን እስከመበተን የሚያደርስ ድንበር ዘለል ወንጀል መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የገቢዎች ሚኒስቴር በ2022 ዓ.ም ሀገራዊ ወጭን በሀገራዊ ገቢ ለመሸፈን እቅድ ይዞ እየሰራ መሆኑን የጠቆሙት ወ/ሮ ዓይናለም፣ ሙስና ይህንን እቅድ ለማሳካት የምናደርገውን ጉዞ የሚፈትን በመሆኑ የጸረ ሙስና ትግሉን አጠናክረን እንቀጥላለንም ብለዋል፡፡

በገቢው ዘርፍ የሚስተዋለውን የሙስና አመለካከትና ተግባር ለመከላከልና ለመቆጣጠር ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ የተለያዩ ስራዎችን እየሰራ መሆኑን ሚኒስትሯ አክለው፣ ለሙስና እና ብልሹ አሰራር በር የሚከፍቱ አደረጃጀቶች እና አሰራሮችን የማሻሻል ስራዎች በቀጣይነት እንደሚተገበሩ አስገንዝበዋል፡፡

የጉምሩክ ኮሚሽን የኦፕሬሽን ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር ወ/ሮ ሙሉወርቅ ደረሰ በበኩላቸው፣ ሙስናን ለመቀነስ ብሎም ለማጥፋት ቅንጅታዊ ስራዎች ወሳኝ መሆናቸውን ተናግረው በዋጋ ትመና፣ በታሪፍ አመዳደብ በኮንትሮባድ እንዲሁም በሌሎች ዘርፎች የሚታዩ ብልሹ አሰራሮችን ለማስወገድ ሁሉም ሰራተኛና አመራር የበኩሉን እንዲወጣ ጠይቀዋል፡፡

የፌደራል የስነ ምግባርና የጸረ ሙስና ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር እሸቴ አስፋው ፤ ኮሚሽኑ ከ20 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ዜጎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ትምህርቶችን መስጠቱን ጠቅሰው ሙስናና ብልሹ አሰራርን የሚጸየፍ ዜጋን ለመፍጠር የትውልድ ስነምግባር ግንባታ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አስረድተዋል፡፡

በውይይት መድረኩ፣ ሙስና በዓለም አቀፍ እና በሀገር አቀፍ ደረጃ እያደረሰ የሚገኘው ዘርፈ ብዙ ጉዳት እንዲሁም በገቢዎች ሚኒስቴር እና በጉምሩክ ኮሚሽን ላይ ያተኮረ የሙስና ስጋት ዳሰሳ ጥናት ቀርቦ ውይይት የተደረገበት ሲሆን በቀጣይም ለሙስናና ብልሹ አሰራር መንገድ የሚከፍቱ ህጎችን የማሻሻል፣ አገልግሎትን የማዘመን እና የቁጥጥር ስርዓትን የማጠናከር ስራዎች ተጠናክረው እንዲቀጥሉም አቅጣጫ ተቀምጧል፡፡

ጉምሩክ ኮሚሽንን የተመለከቱ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/ecczena
በድረ ገጽ፦ www.ecc.gov.et
በቴሌግራም፦ https://t.me/EthiopiaCustomsCommission