Innehållspublicerare

null “ ዛሬ እውቅናና ሽልማት የተበረከተላችሁ ታማኝ ግብር ከፋዮች የዘመናችን አርበኞች ናችሁና ኢትዮጵያ ታመሰግናችኋለች” ፡- ጠ/ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶ/ር)

(ጉምሩክ ኮሚሽን፣ ጥቅምት 2 /2016 ዓ.ም)
አምስተኛው የታማኝ ግብር ከፋዮች የእውቅናና ሽልማት መርሀግብር ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ(ዶ/ር) በተገኙበት ተካሂዷል፡፡
 
በስነስርዓቱ ለታማኝ ግብር ከፋዮች እውቅናና ሽልማት የሰጡት ጠ/ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት ግብርን በታማኝነት መክፈል የሀገር መሰረት መሆኑን ገልጸው ከግብር ከፋዮች በሚሰበሰበው ገቢም በርካታ ሰው ተኮር የልማት ስራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም “ዛሬ እውቅናና ሽልማት የተበረከተላችሁ ታማኝ ግብር ከፋዮች የዘመናችን አርበኞች ናችሁና ኢትዮጵያ ታመሰግናችኋለች” ብለዋል፡፡

“አባቶቻችን በከፈሉት መስዋዕትነት ያልተገዛች ነጻ ሀገር መረከብ ችለናል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ” ባለንበት ዘመን በሁለንተናዊ መልኩ የተሟላ ነጻነትና ክብር ለማግኘትም ሀገራዊ ገቢን ማሳደግ ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የገቢዎች ሚኒስትር ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ በበኩላቸው፣ የገቢ አሰባሰቡን ለማሳደግና በፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ ግብር የመክፈል ባህልን ለማጎልበት ከሚከናወኑ ተግባራት መካከል ለታማኝ ግብር ከፋዮች እውቅና መስጠት አንዱ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

ለአምስተኛ ጊዜ በተካሄደው መርሀግብርም 500 ታማኝ ግብር ከፋዮች እውቅናና ሽልማት እንደተሰጣቸው ሚኒስትሯ ተናግረው ከእነዚህ ውስጥ 50 በፕላቲኒየም፣ 150 በወርቅ፣ 300 በብር ደረጃ እውቅና መሰጠቱን ገልጸዋል፡፡

ጉምሩክ ኮሚሽንን የተመለከቱ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/ecczena
በድረ ገጽ፦ www.ecc.gov.et